Asset Publisher

ታንዛኒያ ሕዳሴ ግድቡ ሁሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገለጸች
ታንዛኒያ ሕዳሴ ግድቡ ሁሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገለጸች
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሁሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ እንደሚያደርግ የታንዛኒያ ፕሬዝዳንት ሳሚያ ሱሉሁ ገለጹ፡፡
በታንዛኒያ የኢትዮጵያ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ሆነው የተሾሙት አምባሳደር ሽብሩ ማሞ የሹመት ደብዳቤያቸውን ለታንዛኒያ ፕሬዝዳንት አቅርበዋል።
አምባሰደሩ የሹመት ደብዳቢቤያቸውን ባቀረቡበት ወቅት የሁለቱን ሀገራት የረጅም ዘመናት ግንኙነትና ቀጣይ የትብብር መስኮችን በሚመለከት ፕሬዝዳንቷ ጋር ሀሳብ ተለዋውጠዋል።
አምባሳደር ሽብሩ በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ እና መንግሥት እየወሰዳቸው ስላለው እርምጃ እንዲሁም ስለ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ገለፃ ማድረጋቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡
በታንዛኒያ እስር ቤት በአስከፊ ችግር ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ተለቀው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱም ጥያቄ አቅርበዋል።
የታንዛኒያ ፕሬዝዳንት ሳሚያ ሱሉሁ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ያጋጠማትን ችግር ለመፍታት መንግሥት እየወሰደ ያለውን እርምጃ እንደሚያደንቁ ተናግረዋል።
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን በሚመለከትም ግድቡ ሁሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት ነው ሲሉም ገልፀዋል።
በአዲስ አበባ የሚገኘውን የታንዛኒያ ኤምባሲ መሬት ጉዳይ በቅርቡ መፍትሔ እንዲያገኝ የኢትዮጵያ መንግሥት ያሳለፈው ውሳኔ እንዳስደሰታቸው የተናገሩት ፕሬዝዳንቷ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ዘመን በማይሽረው ወዳጅነት የተሳሰረ በመሆኑ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በታንዛኒያ እስር ቤት ውስጥ የሚገኙ ዜጎች እንዲለቀቁና ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ለማድረግ መንግሥታቸው ቀና ውሳኔ እንደሚሰጥበትም አረጋግጠዋል።
ፕሬዝዳንት ሳሚያ የታንዛኒያ ዜጎች በኢትዮጵያ አቬሽን ዘርፍ ስልጠና እየወሰዱ መሆናቸውን አንስተው ለዚህም ኢትዮጵያ በዘርፉ ሙያ የአፍሪካ ተምሳሌት መሆኗን በመጥቀስ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል።
ዋልታ ፤ ሰኔ 1/2014