በጁባ ለታላቁ ህዳሴ ግድብና ለሀገር መከላከያ ሠራዊት ከ80 ሺህ ዶላር በላይ ድጋፍ ተሰበሰበ - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ 2ኛ ዙር የውሃ ሙሌት በስኬት መጠናቀቁን ምክንያት በማድረግ በደቡብ ሱዳን (ጁባ) በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አስተባባሪነት “የህዳሴው ግድባችን የህልውናችንና የሉዓላዊነታችን መገለጫ ነው” በሚል መሪ ቃል የድጋፍ መግለጫና የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡
በጁባና አካባቢው የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን በተሣተፉበት በዚህ ፕሮግራም ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ቃል የተገባውን ጨምሮ 64 ሺህ 100 ዶላር እና 25 ሺህ የደቡብ ሱዳን ፓውንድ ተገኝቷል፡፡
ከዚህ ጎን ለጎን ለጀግናው የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድጋፍ የሚሆን 15 ሺህ 100 ዶላር እና 10 ሺህ የደቡብ ሱዳን ፓውንድ ተሰብስቧል፡፡
በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ነቢል ማህዲ በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር በደቡብ ሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሃገራዊና የልማት ጥሪዎችን በከፍተኛ የሀገር ፍቅር ስሜት በመቀበል እያደረጉት ላለው ከፍተኛ ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡
አያይዘውም ኢትዮጵያ በደቡብ ሱዳንና በአጠቃላይ በመላው ዓለም እንደ አምባሳደር ሆነው የሚሰሩላት በሚሊየኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ያሏት ሃገር መሆኗን ተናግረዋል፡፡
ሁሉም ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለሃገራቸው ደህንነትና ልማት በጋራ መቆማቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ እንዲሁም የህዳሴው ግድብ ግንባታ እና የሀገር ህልውና ዘመቻው እስከሚጠናቀቅ የጀመሩትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ አምባሳደር ነቢል ጥሪ ማቅረባቸውን በጁባ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመለክታል፡፡
ምንጭ፡-ኤፍ ቢ ሲ ፣ ሐምሌ 26 ፣ 2013