የህዳሴ ግድብ ውሃ የሚተኛበት 4 ሺህ 854 ሄክታር ደን ሁለተኛው ዙር ምንጣሮ ሊካሄድ ነው - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
የህዳሴ ግድብ ውሃ የሚተኛበት 4 ሺህ 854 ሄክታር ደን ሁለተኛው ዙር ምንጣሮ ሊካሄድ ነው
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴው ግድብ ውሃ የሚተኛበት ስፍራ ሁለተኛ ዙር የደን ምንጣሮ ሊካሄድ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቴክኒክ እና ሙያ ስራ እድል ፈጠራ ኤጀንሲ አስታወቀ።
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ በሽር አብዱራሂም ፤ ሁለተኛውን ዙር የህዳሴውን ግድብ ውሃ ሙሌት ለማከናወን ውሃ የሚተኛበት ቦታ 4 ሺህ 854 ሄክታር ደን ይሸፍናል ብለዋል።
የውሃው መጠንም ከመጀመሪያው ዙር በአራት እጥፍ ከፍ እንደሚል ይጠበቃል ብለዋል፡፡
ኤጀንሲው የደን ምንጣሮውን ለማከናወን በተገባደደው ሳምንት ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ጋር ስምምነት ማድረጉን ገልጸዋል፡፡
በስምምነቱ መሰረት ወጪው ከ81 ሚሊየን ብር በላይ እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡
ምንጣሮውን ለማከናወን ከክልሉ ሁሉም ወረዳዎች የተውጣጡ ከአምስት ሺህ በላይ ስራ አጥ ወጣቶች ካቀፉ 500 ኢንተርፕራይዞች ጋር ኤጀንሲው ውል እየገባ መሆኑንና ይህም በሳምንት እንደሚጠናቀቅ አመልክተዋል፡፡
ለስራው ወጪ ከሚሆነው ገንዘብ ውስጥ 20 በመቶ ቅድመ ክፍያ በቅርቡ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል እንደሚለቀቅ የሚጠበቅ መሆኑን መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የደን ምንጣሮ ስራውን በአንድ ወር ጊዜ ለማጠናቀቅ መታቀዱን አቶ በሽር ገልጸዋል፡፡
ውሃው በሚተኛበት ከግድቡ ግራ እና ቀኝ የሚገኙ ሸርቆሌ፣ ጉባ፣ ወምበራ እና ሰዳል ወረዳዎች የምንጣሮውን ስራ 40 በመቶ እንዲያከናውኑ ይደረጋል ብለዋል፡፡
ቀሪው 60 በመቶ የምንጣሮ ስራ ደግሞ ለሌሎች የክልሉ ወረዳዎች እና ከተማ አስተዳደሮች መከፋሉን አብራርተዋል፡፡
እያንዳንዱ ኢንተርፕራይዝ ዝቅተኛ 10 ሄክታር ከፍተኛው ደግሞ 20 ሄክታር ደን ተረክበው ምንጣሮ እንደሚያከናውኑ ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል፡፡