“ዲያስፖራው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 3 ነጥብ 1 ሚሊዮን ዶላር ለግድቡ ግንባታ አበርክቷል” – ወይዘሮ ሰላማዊት ዳዊት የዲያስፖራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
ዲያስፖራው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 3 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር ለህዳሴው ግድብ ግንባታ ማጠናቀቂያ ማበርከቱን ወይዘሮ ሰላማዊት ዳዊት የዲያስፖራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አስታወቁ።
ዋና ዳይሬክተሯ በተለይም ለአዲስ ዘመን እንዳስታወቁት ፣ ዲያስፖራው በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የነቃ ተሳትፎን እያደረገ ነው ። በተለይም የግድቡ ሥራ በማፋጠን በኩል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ3 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር በላይ የሚሆን ገንዘብን አሰባስቧል።
የኮቮድ 19 ወረርሽኝ እንቅስቃሴውን ያስተጓጉላል የሚል ከፍተኛ ስጋት የነበረ ቢሆንም ዲያስፖራው በተሻለ ሁኔታ አገሩንና ወገኑን እያሰበ ብሎም ባለው ነገር ሁሉ ድጋፉን እያረጋገጠ መሆኑን አመልክተዋል።
በአገራዊ ፕሮጀክቶችና ጥሪዎች ላይም ከዚህ ቀደም ባልተለመደ ሁኔታ በደንብ ተሳትፎን እያደረጉ መሆኑን ያስታወቁት ወይዘሮ ሰላማዊት፣ በተለይም የህዳሴ ግድብን ለመደገፍ እያደረጉ ያሉት ተሳትፎም እጅግ የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።
የህዳሴውን ግድብ ሥራ በመደገፍ በኩል በተለይም ከ2010 እስከ 2012 ዓም ድረስ ያለውን አፈጻጸም እንኳን ብናይ ከዓመት ዓመት ከፍተኛ የሆነ መሻሻል እየታየበት ነው ። ከዛ በፊት ገንዘባችን ተበላ በሚል ይቀርብ የነበረውን ቅሬታ ሁሉ በቀረፈ መልኩ በተለይም በ2012 ዓ.ም እስከ 8 መቶ ሺ የአሜሪካን ዶላር ድረስ በቦንድና በስጦታ ተሰብስቧል ብለዋል።
በያዝነው ዓመትም ይህ ድጋፋቸው በከፍተኛ ሁኔታ ተጠናክሮ ቀጥሏል ያሉት ወይዘሮ ሰላማዊት ፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ 3 ነጥብ 1 ሚሊዮን ዶላር ለግድቡ ግንባታ አበርክቷል ። ይህ ሁኔታ ደግሞ ከፍተኛ የሆነ መነሳሳትን የሚያሳይና ግድቡ ተጠናቆ ለማየትም ያለውን ጉጉት አመላካች መሆኑን ጠቁሟል ።
ዲያስፖራው ለህዳሴ ግድብ ግንባታው ገንዘባቸውን ከማዋጣት ባሻገር በያሉበት አገር ሆነው ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማሲ ሥራዎችን በመስራት ላይ ናቸው ያሉት ወይዘሮ ሰላማዊት፣ ከዚህ ቀደም ባልተለመደ ሁኔታ
በመካከለኛው ምስራቅ አካባቢ ያሉ ሁሉ በአረብኛ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በመጠቀም የኢትዮጵያን አቋም ቁልጭ አድርገው በማስረዳት የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን አስታውቀዋል ።
ባገኙት አጋጣሚና በተገኙባቸው ዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ የኢትዮጵያን አቋም የተቀረው ዓለም እንዲረዳ በማድረግ ግድባችንን እንድናጠናቅቅ እንዲያግዙን ያላሰለሰ ጥረት እያደረጉ መሆኑንም አመልክተዋል።
ኤጀንሲው የዲያስፖራው ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከፍተኛ ጥረት እያደረገ መሆኑን ጠቁመው፣ አሁን ላይ የተለየ እቅድ በማውጣት ከፍ ያለ ውጤትን ለማምጣት እየተሰራ ነው።የማነቃቂያ መልዕክቶችን በመላክ የአገሪቱን ተጨባጭና ትክክለኛ ሁኔታ ተረድተው ከአገራቸው ጎን እንዲቆሙ የሚያስችሏቸውን ሥራዎች በከፍተኛ ሁኔታ በመስራት ላይ ይገኛል ። አገርን በተመለከተ በሚነሱ ጉዳዮች ላይ በቀናነት እንዲሳተፉ ለማድረግ የሚያስችሉ ሥራዎችን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል ።
ዲያስፖራው አገሪቱ የምትፈልገውን የዲፕሎማሲ ሥራ በያሉበት ሆነው እንዲሰሩ ለማስቻል “የዲያስፖራ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ” በሚል ቡድን ተመሰርቶ ዲፕሎማቶቻችንን መሰረት ባደረገ ሁኔታ እየተሰራ ነው። ከ 56 በላይ የሚሆኑ በዓለም አቀፍ ሕጎች ከፍ ያለ እውቀት ያላቸው ዲያስፖራዎችን በመመልመል ህጋዊ በሆነ መንገድ አስፈላጊውን የዲፕሎማሲ ስራ በየአገራቱ እየሰሩ መሆኑን አስታውቀዋል።
ምንጭ፡- አዲስ ዘመን ግንቦት 4 ቀን 2013 ዓ.ም