“የውሃ ሀብት ክፍፍልን የሚመለከቱ ጉዳዮች ሁሉንም የናይል ተፋሰስ አገሮች የሚመለከቱ ናቸው” – አቶ ደመቀ መኮንን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
የውሃ ሀብት ክፍፍልን የሚመለከቱ ጉዳዮች ሁሉንም የናይል ተፋሰስ አገሮች እንደሚመለከት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን አስታወቁ። ሁለተኛው ዙር የህዳሴ ግድብ የውሃ ሙሌት የሶስቱ አገራት ብሄራዊ ገለልተኛ የሳይንቲስቶች ቡድን ባዘጋጀው የውሃ ሙሌት መርሃ ግብር መሰረት እንደሚካሄድ ገለጹ ።
አቶ ደመቀ መኮንን በኦታዋ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ኤምባሲ እና ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ጥምረት በካናዳ በጋራ ባዘጋጁት የዌብናር ስብሰባ ላይ የህዳሴ ግድብን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት ፣ ኢትዮጵያ የዜጎቿን የኃይል ችግር ለመቅረፍና የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የውሃ ሀብቷን መጠቀም ግዴታ እንደሆነ አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ ለናይል ወንዝ 86 በመቶ ድርሻ ያላት እንደመሆኗ መጠን የህዳሴ የግድብ ግንባታን በዚሁ አግባብ መጀመሯን አስታውሰው ፣ ከግድቡ ጋር ተያይዞ በግብጽና በሱዳን በኩል የሚነሱ ስጋቶችን ለመቅረፍ በሶስቱ አገሮች መካከል እ.ኤ.አ በ2015 በተፈረመው የመርሆዎች መግለጫ ስምምነት መሰረት ውይይቶች መካሄዳቸውን አመልክተዋል ። መፍትሔ ባልተደረሰባቸው ጉዳዮች ላይም በአፍሪካ ህብረት አስተባባሪነት ተከታታይ ድርድሮች መደረጋቸውን ጠቁመዋል።
ግድቡ የታችኞቹን የተፋሰሱ አገሮች የጎላ ጉዳት እንደማያመጣ የሚታወቅ ቢሆንም በሱዳን እና በግብጽ በኩል ግን ጉዳዩን ዓለም አቀፍ መልክ እንዲይዝ በማድረጋቸው በአፍሪካ ህብረት አስተባባሪነት የሚካሄደውን ድርድር እያደናቀፉ መሆኑን አስታውቀዋል ። ሁለቱም አገሮች በጋራ እና በፍትሃዊነት ከመጠቀም ይልቅ የቅኝ ገዥዎችን ስምምነት ለማጽናት ያላቸው ፍላጎት ለድርድሩ ሂደት ተግዳሮች እንደሆነ አመልክተዋል።
በአፍሪካ ህብረት አስተባባሪነት የሚደረገው የሶስትዮሽ ድርድር በውሃ ሙሌት እና አስተዳደር ላይ አተኩሮ እንዲቀጥል የኢትዮጵያ ፍላጎት እንደሆነ ገልጸው ፣ ግብጽና ሱዳን ኢትዮጵያ ስምምነት ባለመፈረሟ የድርድር ሂደቱን እንዳስተጓጎለች የሚቀርበው ክስ መሠረት ቢስ መሆኑን አስታውቀዋል።
አጠቃላይ የውሃ ሀብት ክፍፍልን የሚመለከቱ ጉዳዮች ሁሉንም የናይል ተፋሰስ አገሮች የሚመለከት ጉዳይ እንደሆነ ያመለከቱት አቶ ደመቀ፣ ሁለቱ አገሮች አገራችን የወደ ፊት ውሃ የመጠቀም መብትን የሚገድብ አስገዳጅ ውል እንድትገባ የሚያደርጉት ግፊት ተገቢነት እንደሌለውም ገልጸዋል።
በመርሆች ስምምነት መሰረት የውሃ ሙሌቱ የግንባታው አካል በመሆኑ እንዲሁም በሶስት አገሮች ብሄራዊ ገለልተኛ የሳይንቲስቶች ምርምር ቡድኖች በቀረበውና የውሃ አሞላል መርሃ ግብር ስምምነት መሰረት ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት በተያዘለት ጊዜ እንደሚከናወን አረጋግጠዋል።
ምንጭ፡- አዲስ ዘመን ግንቦት 15 ቀን 2013 ዓ.ም