የሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ዕውን እንዳይሆን የሚሹ ሃይሎች አካባቢውን የትርምስ ቀጣና ለማድረግ እየሰሩ ነው - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዕውን እንዳይሆን የሚሹ የውጭ ሃይሎች አካባቢውን የትርምስ ቀጣና ለማድረግ እየሰሩ እንደሆነ የሕዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች አፈ ጉባዔዎች ገለጹ።
የግድቡ መገኛ የሆነው የመተከል ዞን ግጭት የውጭ ሃይሎች እጅ እንዳለበት በመግለጽ ድርጊቱን ኮንነዋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ "በመተከል ዞን ጉባ ወረዳ በግንባታ ላይ የሚገኘው የሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዓይን፣ ልብና መንፈስ ነው" ብለዋል።
የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አደም ፋራህ በበኩላቸው "የሕዳሴውን ግድብ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን አሻራ ያረፈበት የባንዲራ ፕሮጀክት" ብለውታል።
"የግድቡን ግንባታ ለማስተጓጎል የውጭ ሃይሎች ግንባታው የሚገኝበትን የመተከል ዞን የትርምስ ቀጣና ለማድረግ እየሰሩ ነው" በማለትም ኮንነዋል።
በዚህም ከሶስት ዓመት በፊት ከግለሰብ ወደ ብሔር የዞረው የመተከል ግጭት የውጭ ሃይሎች እጅ እንዳለበት ገልጸዋል።
የመተከል ግጭት በዋናነት ከሕዳሴ ግድብ ጋር የተያያዘ መሆኑን ተረድቶ ትንኮሳዎችን ተቋቁሞ ፕሮጀክቱን ዳር ማድረስ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
እነዚህ ሃይሎች ፕሮጀክቱ እንዳይጠናቀቅ ለማድረግ ሙሉ አቅማቸውን በመጠቀም እርስ በርስ ለማጋጨት እየሰሩ መሆኑን በመገንዘብ ኢትዮጵያዊያን በጋራ መቆም እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።
"በአገር ሉዓላዊነት፣ በዜጎችና በአገር ክብር አንደራደርም፤ ታሪክ ምስክር ነው" የሚሉት አፈ ጉባዔዎቹ፤ አሁንም በውሃ ድርድሩ በሉዓላዊነት 'እንደማንደራደር አሳይተናል' ብለዋል።
ኢትዮጵያ በቀጣናው አገራት ሠላም እንደምትሻ፣ ሌሎችን መጉዳት እንደማትፈልግ፣ ሌሎችን ሳትጎዳ በድንበር ተሻጋሪ የውሃ ሀብቷ በመጠቀም ተፈጥራዊ መብቷ እንደማትደራደር መናገራቸውን የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ ሉዓላዊነቷን አስከብራ የቆየች ባለታሪክ ታላቅ አገር መሆኗን ገልጸው፤ ኢትዮጵያውያን የውጭ ሃይሎች በሚፈጥሩት አጀንዳ መጠለፍ እንደሌለባቸውም አስገንዝበዋል።
አንቂዎችና ማኅበራዊ ሚዲያዎች የእርስ በርስ ግጭት የሚያባብሱና ለጠላት ምቹ ዕድል የሚፈጥሩ መረጃዎችን ከማቅረብ እንዲታቀቡም ጠይቀዋል።