“የሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ወደ መጨረሻው ግባችን የሚያስፈነጥረን ነው’’ ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ - መነሻ - am
Nested Portlets
Asset Publisher
Statistics
Web Content Search
Asset Publisher
የሁለተኛውን ዙር የህዳሴ ግድብ ሙሌት ተገባዶ ውሃው በግድቡ አናት ላይ መፍሰሱ ግድቡን ወደ ፍጻሜ ለማድረግ ወደሚሰራው የመጨረሻው የሥራ ምዕራፍ የሚያሸጋግር መሆኑን ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ አስታወቁ።
በተለይም ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት ሁለተኛው የውሃ ሙሌት ማለት 2 ተርባይኖችን ለማንቀሳቀስ የሚያስፈልገውን የውሃ መጠንና ይዘናል ማለት ነው። በቀጣይ የሚተከሉትን ተርባይንና ጄነሬተሮች ኃይል ማመንጨት እንዲችሉ ከፍታቸውን የሚጨምር ነው፤ ይህ ደግሞ የግድቡን ግንባታ መጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንድንደርስ የሚያስፈነጥረን ነው ።
እንደ ኢንጂነር ክፍሌ ገለጻ ግድቡ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዓይን እንደመሆኑ ሥራውን ሰርቶ እዚህ ደረጃ ላይ ለማድረስ ጎን ለጎንም የሚነሱበትን ቅሬታዎች በዲፕሎማሲያዊ አካሄድ መስመር ለማስያዝ ብዙ ጥረቶች ተደርገዋል፤ በዚህም መልካም ውጤቶች በመታየት ላይ ናቸው፤ እነዚህ እንደተጠበቁ ሆነው በትናትናው ዕለት ደግሞ የሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ሥራ መጠናቀቁ ከድል በላይ ነው፤ የግድቡ ፍጻሜም መድረሱን ያመላክታል ብለዋል።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት ስራ በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁ ኢትዮጵያውያን የልፋታቸውን ውጤት ማግኘታቸውን ያመላክታል ያሉት ኢንጂነር ክፍሌ፣ በዚህም መላው ሕዝባችን ከጎናችን ሆነው ያበረታቱን ወዳጆቻችን እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
በፕሮጀክት ላይ ምን ጊዜም ቢሆን ውጤቶች ተራ በተራ ነው የሚገኙት ባለፈው ዓመት የመጀመሪያውን ሙሌት ተጠናቀቀ በዚህ ዓመት ደግሞ ሁለተኛውን ሙሌትና በጥቂት ወራት ውስጥ ደግሞ የኃይል ማመንጨት ስራ ይቀጥላል፤ ከዛ ትልቁና ዋናው ግድብ ፕሮጀክቱን ሙሉ በሙሉ አጠናቆ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማስረከብ ነው ያሉት ኢንጂነር ክፍሌ በመሆኑም ይህ የሙሌት ሥራ የመጨረሻው ግብ ሳይሆን ወደ መጨረሻው ግብ የሚያፈናጥረን መሆኑን መረዳት እንደሚያስፈልግም አብራርተዋል።
የግድቡ ግንባታ በብዙ ተግዳሮቶች የተሞላ ነው ያሉት ኢንጂነር ክፍሌ ለምሳሌ ከጸጥታ መደፍረስ፣ ከመንገድ አለመኖር፣ በሥራው ላይ የተሰማሩ ኮንትራክተሮችን የማስፈራራት ሁኔታዎች ሁሉ ታልፈዋል፤ ከሁሉም የሚበልጠው ግን በዓለም አቀፍ ደረጃ የነበረው ከፍተኛ ጫና ነው ፤ ለእነዚህ ሁሉ ፈተናዎች ሳንበረከክ አልፈን ለዚህ ደረጃ መብቃታችን እጅግ አስደሳች መሆኑንም ጠቁመዋል።
ለዛሬዋ ቀን በመድረሳችን በመጀመሪያ የኢትዮጵያን አምላክ ማመስገን ይገባል ፤ ከዛም ጸሐይ ዝናብ ብድር ሙቀት ሳይሉ ሥራውን በሙሉ ልብና ቁርጠኝነት የሰሩ ባለሙያዎች፣ እስከ አሁኗ ደቂቃ ድረስ አስተዋጿቸው
ላልተጓደለ ኢትዮጵያውያን፣ ለመንግሥት፣ ለመከላከያ ሰራዊት እንዲሁም ሌሎች ምስጋና የሚገባቸው ሁሉ ምስጋና ያስፈልጋቸዋል ብለዋል።
አዲስ ዘመን ሐምሌ 13/2013